
- Main
- Catalog
- Religion & Spirituality
- Advertising on the Telegram channel «ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan»
Advertising on the Telegram channel «ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan»
contet creation
Channel statistics
††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!†††
††† ቅዱስ ፖሊካርፐስ †††
†††ቅዱስ ፖሊካርፐስ:-
*ከ70 እስከ 156 ዓ/ም የነበረ::
*ዮሐንስ ወንጌላዊ በራዕዩ ከመሰከረላቸው 7ቱ አብያተ ክርስቲያናት የአንዱ (የሰርምኔስ) ዻዻስ የነበረ::
*ከሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ቃል በቃል የተማረና ደቀ መዝሙሩ የነበረ አባት ነው::
ታላቁ አግናጥዮስ (ምጥው ለአንበሳ) የዚህ ቅዱስ ባልንጀራ ነበር:: ከ46 ዓመታት በላይ በፍፁም ትጋት ቤተ ክርስቲያንን አገልግሎ አረማውያን በ86 ዓመቱ በአደባባይ በእሳት አቃጥለው ገድለውታል:: አባቶቻችን "ሐዋርያዊ" ሲሉ ይጠሩታል::
††† ዳግመኛ በዚህ ዕለት በ1888 ዓ/ም በቅዱስ ጊዮርጊስ ምልጃና ረዳትነት አባቶቻችን አድዋ ላይ ጣልያንን ድል አድርገዋል:: ቅዱስ ጊዮርጊስን እና ደጉን ንጉሥ ዳግማዊ አፄ ምኒልክን እናስባቸው ዘንድ ይገባል::
††† ቅዱስ አውሳብዮስ ሰማዕት †††
በቤተ ክርስቲያን ስመ ጥር ከሆነ ቅዱሳን ሰማዕታት አንዱ ቅዱስ አውሳብዮስ ነው:: ተወልዶ ያደገው በምድረ አንጾኪያ (ሶርያ) ሲሆን ዘመኑም 3ኛው መቶ ክ/ዘ ነው:: አባቱ ታላቁ ሰማዕት ቅዱስ ፋሲለደስ ነው:: እናቱም ቡርክት ሶፍያ ትባላለች::
ሰማዕቱ ቅዱስ መቃርስ ትንሽ ወንድሙ መሆኑም ይታወቃል:: ቅዱሳን እነ ፊቅጦር : ገላውዴዎስ : ቴዎድሮስ : ዮስጦስ : አባዲር . . . ባልንጀሮቹ ሆነው ኑረዋል::
ቅዱስ አውሳብዮስ የቅዱስ ፋሲለደስ ፍሬ ነውና ጾምና ጸሎትን የሚያዘወትር ሆነ:: በቤተ መንግስት ውስጥ ስንት የተደላደለና የተቀማጠለ ነገር እያለ እርሱ ግን እንደ ቡሩክ አባቱ ንጽሕናን መረጠ:: የወርቅ ካባ ደርቦ ሲሰግዱ ማደር ምን ይደንቅ!
ያ ዘመን እጅግ ግሩም የሆኑ ቅዱሳን በቤተ መንግስት የታዩበት ነበር:: ቅዱስ አውሳብዮስ በምጽዋት : በጾምና ጸሎት የሚኖር ቢሆንም በየጊዜው ወደ ጦርነት ይላክ ነበር:: ምክንያቱም እርሱ ኃያል የጦር ሰው : የሠራዊቱም ሁሉ አለቃ ነውና:: በሔደበት ሁሉም በእግዚአብሔር ኃይል ድል ያደርግ ነበር::
አንድ ጊዜም ከፋርስ ቁዝ ሰዎች ጋር ጦርነት ውስጥ ገቡ:: ይህንን ጦርነት በበላይነት እንዲመሩ ቅዱሳን አውሳብዮስና ዮስጦስ በኑማርያኖስ (ንጉሡ ነው) ተሹመው ወደ ሠልፍ ገቡ::
በጦርነቱ ጐዳና ላይ ሳሉ ግን አንድ አታላይ ሰላይ በጠላት እጅ እንዲወድቁ አደረጋቸው:: የተማረኩና የታሠሩ ዮስጦስና ሠራዊቱ ሲሆኑ ቅዱስ አውሳብዮስ ይህን ሰምቶ አለቀሰ:: ወደ ፈጣሪውም እየተማጸነ ለመነ::
በዚህ ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ አረጋጋው:: ድል መንሳትንም ሰጥቶት አደጋ ጥሎ ባልንጀራውን ዮስጦስን አስፈታው:: ጠላቶቻቸውንም እያሳደዱ አዋረዷቸው:: "ወመጠውከኒ ዘባኖሙ ለጸርየ" እንዳለ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ::
ከዚህ ሠልፍ በሁዋላ ቅዱሳን አውሳብዮስና ዮስጦስ በድል አድራጊነት ወደ አንጾኪያ ሲመለሱ ግን አንጀትን የሚቆርጥ ዜና ደረሳቸው:: አምላከ አማልክት ክርስቶስ ተክዶ ጣዖታት (እነ አዽሎን : አርዳሚስ) እየተሰገደላቸውም ደረሱ:: ይህንን ያደረገ ደግሞ የሰይጣን ታናሹ የሆነ ርጉም ዲዮቅልጢያኖስ ነው::
ቅዱሳኑንም ለጣዖት ስገዱ ሲል በአደባባይ ጠየቃቸው:: ድፍረቱ ያናደደው ቅዱስ አውሳብዮስ ግን ሰይፉን መዞ ወደ ንጉሡ ተራመደ:: ያን ጊዜ ንጉሡ ሸሽቶ ሲያመልጥ መሣፍንቱን ሜዳ ላይ በተናቸው:: አባቱ ቅዱስ ፋሲለደስ ባይገለግለው ኖሮ ኃያል ነውና ባላተረፋቸው ነበር::
ከቀናት በሁዋላ ግን ቅዱስ አውሳብዮስ በጾምና ጸሎት ሰንብቶ ሰማዕት ለመሆን ልቡ ቆረጠ:: ቅዱስ ሚካኤልና አባቱ ፋሲለደስም በምክር አበረቱት:: እርሱም በአጭር ታጥቆ በከሐዲው ንጉሥ አደባባይ ላይ ቆመ::
"እኔ ክርስቲያን ነኝ:: ክርስቶስን አመልካለሁ:: ለእርሱም እገዛለሁ:: ጣዖታት ግን ድንጋዮቸ ናቸውና አይጠቅሙም:: የሚሰግድላቸውም የረከሠ ነው::" ሲል አሰምቶ ተናገረ:: ንጉሡ ዲዮቅልጢያኖስ እዚያው ሊገድለው ፈልጐ ነበር:: ቅዱሱ ተወዳጅ ሰው ነበርና ሁከት እንዳይነሳ አውሳብዮስ ወደ አፍሪቃ (ግብጽ) ሒዶ እንዲገደል ተወሰነበት::
በምድረ ግብጽም አረማውያን በእሳትም : በግርፋትም : በስለትም ብዙ አሰቃዩት:: ቅዱስ ሚካኤል ግን ገነትን አሳይቶ ከደዌው እየፈወሰ ተራዳው:: በመጨረሻም በዚህች ቀን ገድለውት አክሊለ ክብርን ተቀዳጅቷል::
††† አምላከ ቅዱሳን ሰማዕታት ጽናታቸውን አድሎ ከበረከታቸው ይክፈለን::
††† የካቲት 23 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ፖሊካርፐስ ሐዋርያዊ ሰማዕት (የሰርምኔስ ዻዻስ)
2.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት (አባቶቻችንን አድዋ ላይ የረዳበት)
3.ቅዱስ አውሳብዮስ ሰማዕት (የቅዱስ ፋሲለደስ ልጅ)
4.ቅዱስ አውስግንዮስ ሰማዕት
††† ወርኀዊ በዓላት
1.ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት
2.ቅዱስ ሰሎሞን ንጉሠ እስራኤል
3.አባ ጢሞቴዎስ ገዳማዊ
4.አባ ሳሙኤል
5.አባ ስምዖን
6.አባ ገብርኤል
††† "በሰርምኔስም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልዐክ እንዲህ ብለህ ጻፍ:- ሞቶ የነበረው: ሕያውም የሆነው: ፊተኛውና መጨረሻው እንዲህ ይላል:-
'መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ . . . እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን: የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ::" †††
(ራእይ 2:8)
††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
††† ሰማዕትነት በክርስትና ለሃይማኖት የሚከፈል የመጨረሻው ዋጋ (መስዋዕትነት) ነው:: ሰው ለፈጣሪው ሰውነቱን ሊያስገዛ: ሃብት ንብረቱን ሊሰጥ ይችላል:: ከስጦታ በላይ ታላቅ ስጦታ ግን ራስን አሳልፎ መስጠት ነው::
ራስን መስጠት በትዳርም ሆነ በምናኔ ውስጥ ይቻላል:: የመጨረሻ ደረጃው ግን ሰማዕትነት ነው:: "አማን መነኑ ሰማዕት ጣዕማ ለዝ ዓለም: ወተዓገሡ ሞተ መሪረ በእንተ መንግስተ ሰማያት" እንዳለው ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ ሰማዕትነት ማለት መራራውን ሞት ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ሲሉ መታገስ ነው::
እርሱ ቅሉ መድኃኒታችን ክርስቶስ የሰማይና የምድር ጌታ ሲሆን ኃፍረተ መስቀልን ታግሦ ሙቶልን የለ! በዓለም ያሉ ብዙ እምነቶች ስለ መግደል በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ያስተምራሉ:: ክርስትና ግን መሞትን እንጂ መግደልን የሚመለከት ሕግ የለውም::
እርሱ ባለቤቱ "ጠላቶቻችሁን ውደዱ: የሚረግሟችሁን መርቁ: ስለሚያሳድዷችሁ ጸልዩ" ብሎናልና:: (ማቴ. 5:44) ነገር ግን ዕለት ዕለት ራሳችንን በሃይማኖትና በምግባር ካልኮተኮትነው ክርስትና በአንድ ጀምበር ፍጹም የሚኮንበት እምነት አይደለምና በፈተና መውደቅ ይመጣል::
በተለይ የዘመኑ ክርስቲያን ወጣቶች ልናስተውል ይገባናል:: የቀደሙ ወጣት ሰማዕታት ዜና የሚነገረን እንድንጸና ነውና::
ፋርስ (persia) በአሁን መጠሪያዋ "ኢራን" የምትባል: በቀደመው ዘመን የበርካታ እውነተኛ ክርስቲያኖች ቤት ነበረች:: ሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስን ጨምሮ ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድን የመሰሉ አእላፍ ሰማዕታት በዚሕች ሃገር ውስጥ በ2ኛውና 3ኛው መቶ ክ/ዘመን የሰማዕትነት ጽዋዕን ጠጥተዋል:: በ4ኛው መቶ ክ/ዘመንም አባ ማሩና በተባለ ጻድቅ ሰው በዚህች ቀን ዐፅማቸው ተሰብስቦ ቅዳሴ ቤታቸው ተከብሯል::
††† አምላከ ቅዱሳን ይራዳን: ይባርከን: ይቀድሰን:: ከወዳጆቹ በረከትም ያሳትፈን:: የቅዱሳኑን ግፍና መከራ አስቦም ከምንፈራው ጭንቅ ሁሉ ይሰውረን:: ለመንግስቱም ያብቃን::
††† የካቲት 22 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱሳን ሰማዕታተ ፋርስ (ፍልሠታቸውና ቅዳሴ ቤታቸው)
2.ቅዱስ አባ ማሩና ጻድቅ ኤዺስ ቆዾስ (የፋርስ ሰማዕታትን አጽም የሠበሠበ)
3.ቅዱስ አባ ቡላ
††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዑራኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ሉቃስ ወንጌላዊ
3.ቅዱስ ደቅስዮስ (የእመቤታችን ወዳጅ)
4.አባ እንጦንዮስ (አበ መነኮሳት)
5.አባ ዻውሊ የዋህ
††† "ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ: ወይስ ጭንቀት: ወይስ ስደት: ወይስ ራብ: ወይስ መራቆት: ወይስ ፍርሃት: ወይስ ሰይፍ ነውን?
'ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን:: እንደሚታረዱ በጐች ተቆጠርን::'
ተብሎ እንደተጻፈው ነው::
በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን::" †††
(ሮሜ. 8:35-37)
††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
+"+ እንኩዋን ለቅዱስ "አናሲሞስ ሐዋርያ" እና ለእመቤታችን "ቅድስት ድንግል ማርያም" በዓል በሰላም አደረሳችሁ +"+
+*" ድንግል ማርያም "*+
=>የአምላክ እናቱ እመ-ብርሃን ድንግል ማርያም:-
*በ3 ወገን (በሥጋ: በነፍስ: በልቡና) ድንግል
*በ3 ወገን (ከኀልዮ: ከነቢብ: ከገቢር) ንጽሕት
*ሳትጸንስ: በጸነሰች ጊዜና ከጸነሰች በሗላ ድንግል
*ጌታን ሳትወልድ : በወለደችው ጊዜና ከወለደችው በሗላ ድንግል ስትሆን እናትም ድንግልም መሆኗን አምነን እመሰክራለን::
+እመቤታችን ከፍጥረት ሁሉ በላይ ክብርትና ንዕድ ናት:: ሊቃውንት አበው እንዳስተማሩን በዚህ ዕለት እንዲህ ብለን እንጸልያለን::
"ረስዪ ፍና ትሕትና አእጋርየ ይሑሩ:
ትዕቢትሰ ለአምላክ ጸሩ"
(እመቤቴ ሆይ ትዕቢትን አምላክ ይጠላልና እግሮቻችን በትሕትና እንዲሔዱ አድርጊ)
+*" ቅዱስ አናሲሞስ ሐዋርያ "*+
=>በዘመነ ሐዋርያት ምስጉን ከነበሩ አበው አንዱ ቅዱስ አናሲሞስ ነው:: ስለ ቀና አገልግሎቱና መልካም እረኛነቱ አባቶቻችን ሐዋርያት አብዝተው በቀኖናቸው መስክረውለታል:: እርሱ ከኃጢአት ኑሮ ወደ ዘለዓለማዊ የቅድስና ሕይወት መጥቷልና::
¤ይህስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-
=>በሮም ከተማ የሚኖር ፊልሞና የሚባል አንድ ባለጸጋ ነበር:: ይህ ሰው በስብከተ ቅዱስ ዻውሎስ አምኖ ከርስቲያን ሆነና በመንፈሳዊ አገልግሎት ተጠመደ:: ነገር ግን ከአገልጋዮቹ መካከል ያላመነ አንድ ሰው ነበር:: "ተጽዕኖ አላደርግበትም" ብሎ ዝም ይለዋል:: ግን ክርስትና እንዲገባው ለተልዕኮ መንፈሳዊ በሚሔድበት ሥፍራ ያስከትለው ነበር::
+አገልጋዩ ግን በመለወጥ ፈንታ ሌብነትን ለመደ:: ይባስ ብሎም የአሳዳሪውን (የፊልሞናን) ገንዘብ ሠርቆ ወደ ሮም ጠፍቶ ተመለሰ:: ቅዱስ ፊልሞናም ለገንዘቡ ሳይሆን ለሕይወቱ አዘነ::
+ያ ሠርቆ የጠፋው አገልጋይ ግን በሮም ከተማ ሲመላለስ ስብከተ ወንጌልን ይሰማል:: ሰባኪው ደግሞ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ዻውሎስ ነበር:: ቁጭ ብሎ ሲማርም ልቡናው በርቶለት ተጸጸተ:: ከሐዋርያውም ዘንድ ቀርቦ ኃጢአቱን ተናዞ ተጠመቀ::
+ከዚያች ዕለት ጀምሮም ብርቱ ክርስቲያን ሆነ:: በጥቂት ጊዜም የተጋ ሰባኪ : ርሕሩሕ እረኛ ሆነ:: ፈጣሪውንም ደስ አሰኘ:: ነገር ግን ስለ አንድ ነገር ፈጽሞ ያዝን : ይተክዝም ነበር::
+የድሮ አሳዳሪው ቅዱስ ፊልሞና እንዳዘነበት እያወቀ ዝም ማለት ባያስችለው ለመምህሩ ቅዱስ ዻውሎስ ነገረው:: ያን ጊዜም ሐዋርያው በእሥራትና በግርፋት ይሰቃይ ነበር:: በሮም ሳለም አጭር ክታብ (ደብዳቤን) ጽፎ ለዚህ ደቀ መዝሙሩ ሰጠውና ወደ ቀድሞ አሳዳሪው ወደ ፊልሞና ላከው::
+ይህች ጦማር (ክታብ) ዛሬም ድረስ ከ81ዱ አሥራው መጻሕፍት : ከቅዱስ ዻውሎስ 14 መልዕክታት አንዷ ሆና ተቆጥራ እንጠቀምባታለን:: ክታቧ እጅግ አጭር ብትሆንም ምሥጢሯ ግን ሰፊ ነው::
+ያ የተላከ ክርስቲያንም ያችን ክታብ ወስዶ ለቅዱስ ፊልሞና (ለቀድሞ አሳዳሪው) አስረከበ:: ቅዱስ ፊልሞናም በደስታ አቅፎ ሳመው:: ቀድሞውንም ያዘነ በወጣቱ አገልጋይ የነፍስ እዳ እንጂ በገንዘቡ አልነበረምና:: ያ ተላኪ ሰውም በአካባቢው ሲያገለግል ቆይቶ ወደ ቅዱስ ዻውሎስ ተመልሷል:: ደቀ መዝሙሩ ሆኖም ብዙ አገልግሏል::
+#ቅዱስ_አናሲሞስ ማለት . . . የቀድሞ የሰው አገልጋይ . . . ዛሬ የክርስቶስ ባሪያ . . . ቀድሞ ሠራቂ . . . ዛሬ ግን ለመንጋው የሚራራ ሰው የሆነው ይህ ክርስቲያን ነው::
+በ67 ዓ/ም ቅዱስ ዻውሎስ መሰየፉን ተከትሎ እርሱንም አሳድደው : አሰቃይተው : ጭኑንም ሰብረው አሕዛብ ገድለውታል:: በሰማይም የሐዋርያነትና የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጅቷል:: (ጢሞ. 4:6-8, ፊልሞና 1:1-25)
=>አምላከ ቅዱሳን የአናሲሞስን መመለስ : ንስሃና በረከት ያድለን::
=>የካቲት 21 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ አናሲሞስ ሐዋርያ (የቅዱስ ዻውሎስ ሐዋርያ ደቀ መዝሙር ሲሆን ከ14ቱ መልዕክታት አንዱ የሆነው 'ወደ ፊልሞና' የተጻፈው በዚህ ቅዱስ ምክንያት ነው:: ፊል. 1:11)
2.አባ ዘካርያስ ዘሃገረ ስሃ
3.አባ አካክዮስ ጻድቅ
4.አባ ገብርኤል ሊቀ ዻዻሳት
5.አባ ገብርኤል (የኢትዮዽያ ዻዻስ)
=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያም
2.አበው ጎርጎርዮሳት
3.አቡነ ምዕመነ ድንግል
4.አቡነ አምደ ሥላሴ
5.አባ አሮን ሶርያዊ
6.አባ መርትያኖስ ጻድቅ
=>+"+ ስለ ጽዮን ዝም አልልም . . . አሕዛብም ጽድቅሽን ነገሥታትም ሁሉ ክብርሽን ያያሉ:: የእግዚአብሔርም አፍ በሚጠራበት በአዲሱ ስም ትጠሪያለሽ:: በእግዚአብሔር እጅ የክብር አክሊል በአምላክሽም እጅ የመንግሥት ዘውድ ትሆኛለሽ:: +"+ (ኢሳ. 62:1-3)
<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
✞✞✞ እንኩዋን ለጻድቁ "አቡነ ክፍለ ማርያም" እና ለሰማዕቱ ቅዱስ "ፊልሞን መዓንዝር" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞
+*" አቡነ ክፍለ-ማርያም "*+
=>ኢትዮዽያዊው ጻድቅ አቡነ ክፍለ-ማርያም በሐዋርያዊ አገልግሎቱ የተመሠከረለት: ለበርካታ ዓመታት በጾምና በጸሎት በአቱን አጽንቶ የኖረ: ከቅድስናው የተነሳ መላዕክት ሰማያዊ ኅብስት ይመግቡት: ውሃም ከአለት ላይ ይፈልቅለት የነበረ አባት ነው::
+በዘመኑም ረሃብ ነበርና እርሷ ሳታውቀው እናቱን በረሃብ ጠውልጋ ቢያያት በጣም በማዘኑ እንዲባርከው ከቀረበለት የሰንበት ቁርስ ለእናቱ አድልቶ ብዙ ሰጣት:: በዚሕ ምክንያት መልዐኩም ሰማያዊ ኅብስቱን አስቀረበት: ምንጩም ደረቀች::
+ጥፋቱ የገባው አባ ክፍለ-ማርያም ለ11 ዓመታት ንስሃ ገብቶ እግዚአብሔር መልሶለታል:: ከብዙ የገድል ዓመታት በሁዋላም በዚህች ቀን ተሠውሯል::
+*" ቅዱስ ፊልሞን ሰማዕት "*+
=>ይህን ቅዱስ "ፊልሞን መዓንዝር" ብሎ መጥራቱ
የተለመደ ነው:: እርሱ በቀደመ ሕይወቱ አዝማሪ (ዘፋኝ)
ነበርና:: ዘፋኝነት (አዝማሪነት) ደግሞ በክርስትና
ከተከለከሉ ተግባራት አንዱና ዋነኛው በመሆኑ ዘፈን
(ሙዚቃ) መስማትም ሆነ ማድመጡ ኃጢአት ነው::
+ነገር ግን ሁሉ እንዲድን የሚፈቅድ ጌታችን ጥሪውን ወደ
ሁሉም ሰው በየጊዜው ይልካል:: ቅዱስ ፊልሞንም
የክርስቶስ ጥሪ የደረሰው በከንቱ የዘፋኝነት (የአዝማሪነት)
ኑሮ ውስጥ ሳለ ነው:: ነገሩ እንዲህ ነው:-
+በ3ኛው ክ/ዘ መጨረሻ (በ290ዎቹ) አርያኖስ የሚባል
ሹም በግብጽ (እንዴናው) ክርስቲያኖችን ጨፈጨፈ::
ባለማወቅም ክርስቶስን የሚያመልኩ ሚሊየኖችን በሰይፍ
በላቸው:: ከዚህ ድርጊቱ መልስ ደግሞ በጣዖቱ (አዽሎን)
ፊት እያስዘፈነ ከንቱነትን ይሰዋ : ይዝናናም ነበር::
+ከዘፋኞቹ መካከል ደግሞ ይህ ፊልሞን አንዱ ሆኖ
ለዘመናት በፊቱ ተጫወተለት:: አንድ ቀን ግን እንዲህ
ሆነ:: አስቃሎን የሚባል ቅዱስ ክርስቲያን ለጣዖት
እንዲሰዋ ታዘዘ::
+ይህ አስቃሎን (አብላንዮስም ይባላል) ወንድሙን
ፊልሞንን ያድነው ዘንድ ተጠበበ:: ወደ ፊልሞን ሒዶ "እኔ
ገንዘብ እሰጥሃለሁ:: የእኔን ልብስ ለብሰህ : እኔን መስለህ
ለጣዖት ሰዋልኝ" አለው:: አስቃሎን ይህንን ያለው
ለጥበቡ ሲሆን ፊልሞን ግን "ገንዘብ ካገኘሁ" ብሎ
የባልንጀራውን ልብስ ተሸፋፍኖ ወደ ጣዖቱ ፊት ቀረበ::
+ያን ጊዜ ተሸፍኖ መስዋዕት ማቅረብ ክልክል ነውና ሹሙ
አርያኖስ ግለጡት ሲል አዘዘ:: ቢገልጡት ፊልሞን ሁኖ
ተገኘ:: መኮንኑ ገርሞት "ምን እያደረክ ነው?" ቢለው "እኔ
ክርስቲያን ነኝ" ሲል አሰምቶ ተናገረ::
+ለጊዜው ሁሉም እየቀለደ መስሏቸው ነበር:: ፊልሞን
ግን ይህንን ያለው ከልቡ ነው:: ምክንያት በቅዱስ
አስቃሎን ልብስ ተመስሎ መንፈስ ቅዱስ ልቡን ለውጦለት
ነበር:: ተገልጦ ቀና ሲልም ቅዱሳን መላእክት ከበውት
አይቶ ልቡ ጸንቶለታል::
+ሹሙ አርያኖስም የቀልዱን እንዳልሆነ ሲያውቅ
"ታብዳለህ?" ቢለው ፊልሞን "ምን አብዳለሁ! ዛሬ ገና
ከእብደቴ ሁሉ ዳንሁ እንጂ" ሲል መልሶለታል:: አሕዛብ
ሁሉ እያዩም በዚያች ቅጽበት መንፈስ ቅዱስ በደመና
አምሳል ወርዶ አጥምቆታል::
+በሆነው ሁሉ የተበሳጨው ሹሙም ቅዱስ ፊልሞንን
ከክርስቶስ ፍቅር ይለየው ዘንድ ደበደበው : ገረፈው :
ጥርሱን አረገፈው : ደሙንም መሬት ላይ አፈሰሰው::
በዚህ ሁሉ ግን ጸና:: ቅዱስ አስቃሎንም ፈጥኖ መጥቶ
በመከራው መሰለው::
+በመጨረሻም 2ቱም ቅዱሳን በቀስት ተነድፈው ይገደሉ
ዘንድ ተፈረደባቸው:: ነገር ግን ለእነሱ የተወረወረ ቀስት
መንገዱን ስቶ የሹሙን (የአርያኖስን) ዐይን በማጥፋቱ
ወታደሮቹ በንዴት 2ቱንም ሰይፈው ገድለዋቸዋል::
+ዐይኑ የጠፋበት አርያኖስም ስቃዩ ሲበዛበትና
ከሚያመልካቸው የረከሱ ጣዖታት መፍትሔ ሲያጣ
ከቅዱሳኑ ደም ተቀባ:: ዐይኑም ፈጥኖ በራለት:: በዚህም
ምክንያት ምድራዊ ሹመቱን : ሃብት ንብረቱን : ትዳርና
ቤቱን : ጣዖት አምልኮውን ትቶ በክርስቶስ አምኖ
ለሰማዕትነት በቅቷል::
=>አምላከ ቅዱሳን በወዳጆቹ አማላጅነት
የምናስተውልበትን አዕምሮ አይንሳን:: በረከታቸውንም
ያድለን::
=>የካቲት 20 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.አቡነ ክፍለ-ማርያም ዘዲባጋ (የተሰወረበት)
2.አቡነ ገብረ-መርዐዊ ዘአግዶ (ኢትዮዽያዊ)
3.ቅዱስ ፊልሞን መዐንዝር (ከአዝማሪነት በክርስቶስ አምኖ ለሰማዕትነት የበቃ ቅዱስ ሰው)
4.ቅዱስ አስቃሎን አናጉንስጢስ (ሰማዕት)
5.ቅዱስ ዼጥሮስ ሊቀ ዻዻሳት (የታላቁ ሐዋርያዊ አትናቴዎስ ደቀ መዝሙር)
=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ቴዎድሮስ ሊቀ ሠራዊት (ሰማዕት)
2.ቅዱስ ዮሐንስ ሐፂር
3.ቅዱስ አክሎግ ቀሲስ
4.ቅዱስ አፄ ካሌብ ጻድቅ
5.አባ አሞንዮስ ዘሃገረ ቶና
6.ቅድስት ሳድዥ የዋሒት
=>+"+ ስትጦሙም እንደ ግብዞች አትጠውልጉ . . . አንተ ግን ስትጦም በስውር ላለው አባትህ እንጂ እንደ ጦመኛ ለሰዎች እንዳትታይ ራስህን ተቀባ: ፊትህንም ታጠብ:: በስውር የሚያይ አባትህም በግልጥ ያስረክብሃል:: +"+ (ማቴ. 6:16)
<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
Reviews channel
- Added: Newest first
- Added: Oldest first
- Rating: High to low
- Rating: Low to high
Catalog of Telegram Channels for Native Placements
Advertising on the Telegram channel «ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan» is a Telegram channel in the category «Религия и духовность», offering effective formats for placing advertising posts on TG. The channel has 13.5K subscribers and provides quality content. The advertising posts on the channel help brands attract audience attention and increase reach. The channel's rating is 27.5, with 1 reviews and an average score of 5.0.
You can launch an advertising campaign through the Telega.in service, choosing a convenient format for placement. The Platform provides transparent cooperation conditions and offers detailed analytics. The placement cost is 30.0 ₽, and with 1 completed requests, the channel has established itself as a reliable partner for advertising on Telegram. Place integrations today and attract new clients!
You will be able to add channels from the catalog to the cart again.
Комментарий