
- Main
- Catalog
- Religion & Spirituality
- Advertising on the Telegram channel «ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan»
Advertising on the Telegram channel «ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan»
contet creation
Channel statistics
+*" ኖላዊ ሔር "*+
=>እግዚአብሔር አዳምን በ7 ሃብታት አክብሮ በገነት ቢያኖረው "አትብላ" የተባለውን ዕፀ በለስ በላ:: በዚህም ከፈጣሪው ተጣልቶ: በሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ: በርደተ መቃብር ርደተ ገሃነም ተፈረደበት:: በሁዋላ ግን ንስሃ ስለ ገባ "ከ5 ቀን ተኩል (5,500 ዘመን) በሁዋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ቃል ኪዳንን ሰጠው::
+ከዚህ በሁዋላ ለ5,500 ዘመናት ጊዜ ወደ ታች ይቆጠር ጀመር:: ስለ እግዚአብሔር ሰው መሆንና ዓለምን ማዳንም ትንቢት ይነገር: ሱባኤ ይቆጠር: ምሳሌም ይመሰል ገባ::
+ከአዳም እስከ ሙሴ (ዘመነ አበው) ምሳሌያት ይበዛሉ:: ከሙሴ እስከ ዳዊት (ዘመነ መሣፍንት) ምሳሌያቱ እየጐሉ መጥተዋል:: ከልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት እስከ ቅዱስ ሚልክያስ ድረስ (በዘመነ ነቢያት / ነገሥት) ግን ትንቢቶች ስለ ክርስቶስና ስለ ማደሪያ እናቱ እንደ ጐርፍ ፈሰዋል::
+ነቢያትም የመሲህን መምጣት እየጠበቁ በጾም: በጸሎትና በትሕርምት ኑረዋል:: እንባቸውንም አፍሰው ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶላቸዋል::
=>ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህችን ዕለት "ኖላዊ ሔር" ብላ ታከብራለች:: ይሕንንም ለሳምንት ያህል ታዘክራለች:: መሠረታዊ መነሻዋም (ዮሐ. 10:1) ነው:: "ኖላዊ" ማለት በቁሙ "እረኛ" ማለት ሲሆን "ሔር" ደግሞ "ቸር-ርሕሩሕ-አዛኝ" እንደ ማለት ነው::
+ገጥመን ብንተረጉመው ደግሞ "ቸር እረኛ" የሚል ትርጉምን ይሰጠናል:: ከአባታችን አዳም ስህተት በሁዋላ ተፈጥረው ከነበሩ ችግሮች አንዱ ቸር እረኛ ማጣት ነው:: እግዚአብሔር አዳምን ፈጥሮ: ቸር እረኛ ሆኖ በገነት አሰማርቶት ነበር::
+ኤዶም ገነት የለመለመች: ፈሳሾች የሞሉባት መልካም መስክ ናትና:: አባታችን ቅዱስ አዳም ደግሞ እንደ አቅሙ የጸጋ እረኝነት ተሰጥቶት ነበር:: ድቀት ካገኘው በሁዋላ ግን ከነፍስ እረኛው ጋር ተጣልቶ ከመልካሟ መስክ ገነት ወጣ::
+እርሷንና የነፍሱን እረኛ ሲሻም አለቀሰ:: ተስፋ ድኅነት ሲሰጠውም ለልጆቹ ነገራቸው:: ከዚያም በመንጋው ላይ በአዳም ሴት ተተካ:: ከሴት ኄኖስ: ከኄኖስ: ቃይናን . . . እያለ ከኖኅ ደረሰ::
+ከኖኅም በሴም ከአብርሃም: ከአብርሃምም በይስሐቅና በያዕቆብ ወርዶ ከሙሴ ደረሰ:: ከሙሴም በኢያሱ አልፎ ከነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ደረሰ:: እነዚህ ሁሉ እረኞች ምንም እንኩዋ ለእግዚአብሔር ሕዝብ በትጋት ቢሠሩም ሕዝቡን ከሲዖል ማዳን አልቻሉም::
+ከሲዖል የሚያድን የነፍስ እረኛ ነውና ያን ጊዜ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት የራሱን: የአባቶቹንና የልጆቹን ጩኸት ባንድ አድርጐ ጮኸላቸው:: "ኖላዊሆሙ ለእሥራኤል አጽምዕ - የእሥራኤል እረኛ ሆይ ስማን!" አለ:: (መዝ. 79:1)
+ጩኸቱም ቅድመ እግዚአብሔር ደረሰ:: ይህንን የሰማ ጌታም በጊዜው ከድንግል ማርያም ተወለደ:: በየጥቂቱ አድጐ ቸር እረኝነቱን ገለጠ:: መድኃኒታችን እንዳስተማረን እርሱ ቸር እረኛ ነው::
+ከእርሱ በፊት የተነሱት ቴዎዳስ ዘግብጽና ይሁዳ ዘገሊላ (ሐዋ. 5:36, ዮሐ. 10:8) ሐሰተኛ እረኞች ነበሩ:: እርሱ ግን እውነተኛው የበጐች በር ነውና (ዮሐ. 10:7) በእርሱ የሚገቡ ሁሉ የዘለዓለም ሕይወትን ያገኛሉ::
+እርሱ እውነተኛ እረኛ ነውና (ዮሐ. 10:11) ለመንጋው ራሱን አሳልፎ ይሰጣል:: በእሥራኤል ባሕል እረኞች ከፊት: መንጋው (በጐቹ) ከሁዋላ ሆነው ይሔዳሉና ገዳይ ቢመጣ መጀመሪያ የሚገድለው እረኛውን ነው::
+መድኃኒታችን ክርስቶስ በሞቱ ሕይወትን: በመራቆቱ የጸጋ ልብስን: በውርደቱ ክብርን: በድካሙ ኃይልን ይሰጠን ዘንድ ስለ እኛ ራሱን አሳልፎ ሰጠ:: የማይሞት ንጉሥ ስለ መንጋው ሞተ:: ሰማይን ከነግሡ ምድርንም ከነልብሱ የፈጠረ ጌታ (ዘፍ. 1:1, ዮሐ. 1:2) ስለ በጐቹ ይህንን ሁሉ ታግሦ ከሲዖል አዳነን::
+በሚያርግ ጊዜም በእርሱ ፈንታ ባለ ሙሉ ስልጣን እረኞችን: ሐዋርያትን (ዮሐ. 21:15) ሊቃነ ዻዻሳትን (ሐዋ. 20:28) ካህናትን (ማቴ. 18:18) ሾመልን:: እነርሱን እረኞች አሰኝቶ እርሱ "ሊቀ ኖሎት-የእረኞች አለቃ" ተባለ:: እነርሱም እስከ ዓለም ፍጻም የክርስቶስን መንጋ ሊጠብቁ ስልጣኑም: ኃላፊነቱም አለባቸው:: (ማቴ. 28:19)
+*" ቅዱስ በርናባስ ሐዋርያ "*+
=>ቅዱሱ ሐዋርያ ስሙ ሲጠራ ሞገስ አለው:: የቅዱሱ ሰው የመጀመሪያ ስሙ ዮሴፍ ሲሆን በርናባስ ያለው መድኃኒታችን ክርስቶስ ነው:: ትርጉሙም "ወልደ ኑዛዜ-የመጽናናት ልጅ" እንደ ማለት ነው::
+በምሥጢሩ ግን "ማሕደረ መንፈስ ቅዱስ-የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ" እንደ ማለት ያስተረጉማል:: ቅዱስ በርናባስ ምንም በትውልዱ እሥራኤላዊ ቢሆን ተወልዶ ያደገው በቆዽሮስ ነው:: እስከ ወጣትነት ጊዜውም የቆየው እዚያው ነው::
+የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የመሆኑ ዜና ሲሰማ ግን ወደ ኢየሩሳሌም መጥቶ መድኅን ክርስቶስን ተመለከተ:: ጌታውንም ሊከተል በልቡ ቆረጠ:: የፈጠረን ክርስቶስም እንዲረባ (እንዲጠቅም) አውቆ: ስሙን ቀይሮ አስከተለው:: ከ72ቱ አርድእትም ደመረው::
+ቅዱስ በርናባስ እንደ ወንድሞቹ ሐዋርያት ለ3 ዓመት ከ3 ወር ከጌታ እግር ቁጭ ብሎ ተማረ:: ተአምራቱንም ሁሉ ተመለከተ:: ከጌታ ዕርገት በሁዋላ 120ው ቤተሰብ በጽርሐ ጽዮን ሲጸልዩም አብሮ ይተጋ ነበር::
+በጊዜውም አበው ሐዋርያት በይሁዳ ፈንታ ከ12ቱ የሚቆጠረውን ሰው ለመምረጥ 2 ሰዎችን አቅርበው ነበርና አንዱ ይኸው ቅዱስ ነው:: እዚያውም ላይ ጌታችንን ከመጀመሪያው ጀምሮ ማገልገሉ ተመስክሮለታል:: (ሐዋ. 1:22)
+ስሙንም ኢዮስጦስ ብለውታል:: ባለ 3 ስም ነበርና:: በወቅቱም ዕጣ በቅዱስ ማትያስ ላይ ስለ ወደቀ በርናባስ ከ72ቱ አርድእት: ማትያስ ከ12ቱ ሐዋርያት ሆነው ቀጠሉ::
+ከዚህ በሁዋላ ቅዱስ በርናባስ መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ በኃይል ያገለግል ጀመር:: የሐዋርያትን ዜና በሚናገር መጽሐፍ ላይ የተጻፉና ስለ ቅዱሱ ማንነት የሚናገሩ ክፍሎችን እንመልከት::
1.ቅዱሳን ሐዋርያት የእኔ የሚሉት ንብረት ሳይኖራቸው: ያላቸውን በጋራ እየተጠቀሙ በፍቅር ይኖሩ ዘንድ የመንፈስ ቅዱስ ትዕዛዝ ነበር:: ያለውን ሁሉ ሸጦ በሐዋርያት እግር ላይ በማኖር ደግሞ ቀዳሚውን ሥፍራ ቅዱስ በርናባስ ይይዛል:: (ሐዋ. 4:36) በዚህም የዘመነ ሐዋርያት የመጀመሪያው መናኝ ተብሏል::
2.ልሳነ እፍረት (ብርሃነ ዓለም) ቅዱስ ዻውሎስ ባመነ ጊዜ ሐዋርያት ለማመን ተቸግረው ነበር:: የሆነውን ሁሉ አስረድቶ ቅዱስ ዻውሎስን ከሐዋርያት ጋር የቀላቀለው ይህ ቅዱስ ነው:: (ሐዋ. 9:26)
3.አንድ ቀን መንፈስ ቅዱስ "ፍልጥዎሙ ሊተ ለሳውል ወለበርናባስ - በርናባስና ሳውልን (ዻውሎስን) ለዩልኝ" በማለቱ ሐዋርያት ጾመው: ጸልየው: እጃቸው ከጫኑባቸው በሁዋላ ላአኩአቸው:: (ሐዋ. 13:1)
+እነርሱም ወንጌልን እየሰበኩ በየሃገሩ ዞሩ:: በሃገረ ልስጥራን መጻጉዕን ስለ ፈወሱ ሕዝቡ "እናምልካችሁ" ብለው የአማልክትን ስም አወጡላቸው:: 2ቱ ቅዱሳን ግን ይህንን ሲሰሙ ልብሳቸውን ቀደው በጭንቅ አስተዋቸው:: መመለክ የብቻው የፈጣሪ ገንዘብ ነውና:: (ሐዋ. 14:8-18, ዘጸ. 20:1)
4.በአንጾኪያ የነበሩ አሕዛብ ክርስትናን በተቀበሉ ጊዜ ከሐዋርያት ተልኮ ሒዶ በጐ ጐዳናን መራቸው:: (ሐዋ. 11:22)
+ቅዱሱ ከብዙ ትጋት በሁዋላ በዚህች ቀን አረማውያንና አይሁድ ገድለውታል:: ቅዱስ ማርቆስም ገንዞ ቀብሮታል::
<< ስለርሱ መጽሐፍ "ደግ: መንፈስ ቅዱስ የሞላበት ነው" ይላልና ክብር ይገባዋል !! >> (ሐዋ. 11:24)
+"+ አባ ይስሐቅ ጻድቅ +"+
=>ይህ ቅዱስ በመካከለኛው ዘመን በምድረ ግብጽ የነበረ ገዳማዊ ነው:: መንኖ ለብዙ ዘመናት በገዳም ሲኖር ምኞቱ አንዲት ብቻ ነበረች:: እመቤታችንን በአካል መመልከትን ይፈልግ ነበር::
+የገዳሙ ጠባቂ በመሆኑ መነኮሳት ሲተኙ መቅደሱን ከፍቶ በድንግል ማርያም ስዕል ፊት ይጸልይ: ይሰግድ: ያነባ ነበር:: እንዲህ ለ7 ዓመታት ስለ ተጋ ድንግል እመ ብርሃን ልመናውን ሰማች::
+በዚህ ዕለትም ከፀሐይ 7 እጅ ደምቃ ወደ እርሱ መጣች:: ደንግጦ ሲወድቅ አነሳችው:: "ከ3 ቀናት በሁዋላ እመለሳለሁ" ብላም ተሠወረችው:: በ23ም ዐረፈ::
"በዛቲ ዕለት ሶበ ጸለየ ጥቡዐ::
ለይስሐቅ አስተርዓየቶ እም አይቆናሃ ወጺአ::
እምጸዳለ መብረቅ ጥቀ እንዘ ትጸድል ስብአ::" እንዳለ ደራሲ:: (አርኬ)
=>የእሥራኤል እረኛ ሥጋችንን ከመቅሰፍት: ነፍሳችንን ከገሃነመ እሳት ይጠብቅልን:: ከበረከተ ቅዱሳንም ይክፈለን::
=>ታሕሳስ 21 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ኖላዊ ሔር
2.ቅዱስ በርናባስ ሐዋርያ
3.አባ ይስሐቅ ጻድቅ
=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅድስት ድንግል እግዝእትነ ማርያም
2.አበው ጎርጎርዮሳት
3.አቡነ ምዕመነ ድንግል
4.አቡነ አምደ ሥላሴ
5.አባ አሮን ሶርያዊ
6.አባ መርትያኖስ ጻድቅ
=>+"+ መልካም እረኛ እኔ ነኝ:: አብም እንደሚያውቀኝ: እኔም አብን እንደማውቀው የራሴን በጐች አውቃለሁ:: የራሴም በጐች ያውቁኛል:: ነፍሴንም ስለ በጐች አኖራለሁ:: ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጐች አሉኝ:: እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል:: ድምጼን ይሰማሉ:: አንድም መንጋ ይሆናሉ:: +"+ (ዮሐ. 10:14)
<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
+*" ቅዱስ ሐጌ ነቢይ "*+
=>ነቢይ ማለት በቁሙ ኃላፍያትን (አልፎ የተሠወረውን ምሥጢር) : መጻዕያትን (ገና ለወደ ፊት የሚሆነውን) የሚያውቅ ሰው ማለት ነው:: ሃብተ ትንቢት የእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቡ ሲሆን እርሱ ለወደደው ደግሞ በጸጋ ይሰጠዋል:: እነዚህም ከጌታ ሃብተ ትንቢት የተሰጣቸው አባቶችና እናቶች "ቅዱሳን ነቢያት" በመባል ይታወቃሉ::
+"ዘመነ ነቢያት" ተብሎ የሚታወቀው ብሉይ ኪዳን ቢሆንም እስከ ምጽዓት ድረስ ጸጋውን እግዚአብሔር ለፈቀደላቸው አይነሳቸውም:: በሐዋርያት መካከልም ቅዱስ አጋቦስን የመሰሉ ነቢያት ነበሩ:: (ሐዋ. 11:27) ቅዱሳን ነቢያት ከእግዚአብሔር እየተላኩ ሰውን ከፈጣሪው እንዲታረቅ ይመክራሉ: ይገስጻሉ::
+ከበጐ ሃይማኖታቸውና ንጽሕናቸው የተነሳም እግዚአብሔርን በተለያየ አርአያና አምሳል አይተውታል::
"እስመ በአንጽሖ መንፈስ ርዕይዎ ነቢያት ለእግዚአብሔር: ወተናጸሩ ገጸ በገጽ" እንዳለ አባ ሕርያቆስ:: (ቅዳሴ ማርያም)
+የብዙ ነቢያት ፍጻሜአቸው መከራን መቀበል ነው:: እውነትን ስለ ተናገሩ: አንዳንዶቹም በእሳት: አንዳንዶቹም በሰይፍ: አንዳንዶቹም በመጋዝ ተፈትነዋል:: ሌሎቹ ለአናብስት ሲጣሉ ቀሪዎቹ ደግሞ በድንጋይ ተወግረዋል::
+ስለዚህም መከራቸው ለቤተ ክርስቲያን መሠረት ተብለዋል:: ጌታም ለደቀ መዛሙርቱ "ሌሎች ደከሙ: እናንተ በድካማቸው ገባችሁ" ብሎ የነቢያቱን መከራ ተናግሯል:: (ዮሐ. 4:36)
+ነቢያት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስና እና ድንግል እናቱን ለማየት ብዙ ጥረዋል: ሽተዋልም:: "ብዙ ነቢያትና ጻድቃን እናንተ የምታዩትን ሊያዩ ሹ" እንዳለ ጌታ በወንጌል:: (ማቴ. 13:16, 1ዼጥ. 1:10) ዛሬ ግን በሰማያት ጸጋ በዝቶላቸው : ክብር ተሰጥቷቸው ሐሴትን ያደርጋሉ::
+ቅዱሳን ነቢያት በዋነኝነት "15ቱ አበው ነቢያት" : "4ቱ ዐበይት ነቢያት" : "12ቱ ደቂቀ ነቢያት" ና "ካልአን ነቢያት" ተብለው በ4 ይከፈላሉ::
=>"15ቱ አበው ነቢያት" ማለት:-
*ቅዱስ አዳም አባታችን
*ሴት
*ሔኖስ
*ቃይናን
*መላልኤል
*ያሬድ
*ኄኖክ
*ማቱሳላ
*ላሜሕ
*ኖኅ
*አብርሃም
*ይስሐቅ
*ያዕቆብ
*ሙሴና
*ሳሙኤል ናቸው::
=>"4ቱ ዐበይት ነቢያት"
*ቅዱስ ኢሳይያስ ልዑለ ቃል
*ቅዱስ ኤርምያስ *ቅዱስ ሕዝቅኤልና
*ቅዱስ ዳንኤል ናቸው::
=>"12ቱ ደቂቀ ነቢያት"
*ቅዱስ ሆሴዕ
*አሞጽ
*ሚክያስ
*ዮናስ
*ናሆም
*አብድዩ
*ሶፎንያስ
*ሐጌ
*ኢዩኤል
*ዕንባቆም
*ዘካርያስና
*ሚልክያስ ናቸው::
=>"ካልአን ነቢያት" ደግሞ:-
*እነ ኢያሱ
*ሶምሶን
*ዮፍታሔ
*ጌዴዎን
*ዳዊት
*ሰሎሞን
*ኤልያስና
*ኤልሳዕ ሌሎችም ናቸው::
=>ነቢያት በከተማም ይከፈላሉ::
*የይሁዳ (ኢየሩሳሌም):
*የሰማርያ (እሥራኤል)
*የባቢሎን (በምርኮ ጊዜ) ተብለው ይጠራሉ:: በዘመን አከፋፈል ደግሞ:-
*ከአዳም እስከ ዮሴፍ (የዘመነ አበው ነቢያት):
*ከሊቀ ነቢያት ሙሴ እስከ ነቢዩ ሳሙኤል (የዘመነ መሳፍንት ነቢያት)
*ከቅዱስ ዳዊት እስከ ዘሩባቤል ያሉት (የዘመነ ነገሥት ነቢያት):
*ከዘሩባቤል ዕረፍት እስከ መጥምቁ ዮሐንስ ያሉት ደግሞ (የዘመነ ካህናት ነቢያት) ይባላሉ::
+ስለ ቅዱሳን ነቢያት በጥቂቱ ይህንን ካልን ወደ ዕለቱ በዓል እንመለስ::
+ቅዱስ ሐጌ ቁጥሩ ከ12ቱ ደቂቀ ነቢያት ሲሆን ዘመነ ትንቢቱም ቅ.ል. ክርስቶስ በ450 ዓ/ዓ አካባቢ ነው:: "ደቂቀ ነቢያት" ማለት በጥሬው "የነቢያት ልጆች" ማለት ነው:: አንድም የጻፏቸው ትንቢቶች ሲበዙ 14 ምዕራፍ: ሲያንስ አንድ ምዕራፍ ያላቸው ናቸው::
=>"ሐጌ" ማለት መልአከ እግዚአብሔር (የእግዚአብሔር መልእክተኛ) ማለት ነው:: አንዳንዴም "በዓል" ተብሎ ይተረጐማል:: ትውልዱ ከነገደ ጋድ ሲሆን አባቱ አግታ: እናቱ ሲን ይባላሉ::
+በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ከደኃርት (ከሁዋለኛው ዘመን ነቢያት) አንዱ ነው ይባላል:: ቁጥሩም ከ12ቱ ደቂቀ ነቢያት ነው:: ጥንተ ነገሩስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-
+እሥራኤል ከተከፈለችበት ከመንግስተ ሮብዓም (ከክርስቶስ ልደት 931 ዓመታት በፊት) በሁዋላ 10ሩ ነገድ "እሥራኤል": 2ቱ ነገድ "ይሁዳ" ተብለው በሰሜንና በደቡብ አቅጣጫ ተለያዩ:: መናገሻቸውም ኢየሩሳሌምና ሰማርያ ሆኑ::
+ከዕለት ዕለት ግን የሁሉም ኃጢአት እየበዛ በመሔዱ እግዚአብሔር አዘነባቸው:: ለአሕዛብም አሳልፎ ሰጣቸው:: አስቀድሞ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በ722 ዓመት የአሦሩ ንጉሥ ስልምናሶር መጥቶ ሰማርያን አጠፋት:: 10ሩን ነገድም በባርነት አሦር አወረዳቸው::
+ከዚህ ትምሕርት መውሰድ የተሳናቸው 2ቱ ነገድም ሊገሰጹ አልቻሉምና ተመሳሳይ ዕጣ ደረሰባቸው:: የእግዚአብሔርንና የነቢያቱን ድምጽ: ይልቁኑ የኤርምያስን ምክር አልሰሙምና ከክርስቶስ ልደት 586 ዓመታት በፊት ኃይለኛው የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነጾር መጣ::
+የሚገድለውን ገድሎ: ሕዝቡንም ማርኮ ወደ ፋርስ ባቢሎን ሲያወርዳቸው ኢየሩሳሌምን ምድረ በዳ አደረጋት:: (2ነገ. )
+እግዚአብሔርን የማይሰማ ሕዝብ ምን ጊዜም እጣ ፈንታው ይሔው ነው:: በተለይ ብዙ ጊዜ የእግዚአብሔር ቸርነት የበዛለት ሕዝብ እንዲህ አንገተ ደንዳና ሲሆን ይገርማል:: በእርግጥ ዛሬ እስራኤል ያይደለ ሃገረ እግዚአብሔር ኢትዮዽያ ናትና ከመሰል መከራ ለመራቅ ድምጹን መስማት ያስፈልጋል::
+ሕዝቡ ግን ፋርስ : ባቢሎን ወርደው መከራን ሲቀበሉ : ነቢያት ያሉት ሁሉ ሲፈጸምባቸው ተጸጸቱ:: ፈጣሪም ተስፋ እንዳይቆርጡ በዚያው ዳንኤልን የመሰሉ ነቢያትን አስነሳላቸው:: እነ ኤርምያስንም ከግብጽ ላከላቸው::
+ሕዝቡም (በተለይ "ትሩፋን" የተባሉት) "እግዚአብሔር ሆይ! 'ወሰብዓ ዓም ኃሊቆ' ባልከው ቃልህ : 70ው ዘመን ሲፈጸም ወደ አባቶቻችን ርስት ብትመልሰን መቅደስህን እናንጻለን:: በጐ ምግባርን እንይዛለን" ሲሉ ተሳሉ::
+ልመናን የሚሰማ ቸሩ ፈጣሪም እንደ ቃሉ 70ው ዘመን ሲፈጸም እሥራኤል በነ ኤርምያስ ባሮክና እና ሌሎችም አማካኝነት በኃይል: በድንቅና በተአምራት ከፋርስ ባቢሎን ወጡ:: በድል ተጉዘውም ወደ ርስታቸው ገቡ::
+የሰው ነገር አስቸጋሪ ነውና ከርስታቸው ከገቡ በሁዋላ ግን ስዕለታቸውን ሳይፈጽሙ ቀሩ:: በዚህ ጊዜም እንደ ዘወትሩ ይገሥጻቸው ዘንድ እግዚአብሔር ነቢያቱን ሐጌን : ዘካርያስንና ሚልክያስን አስነሳቸው::
+ሕዝቡ "እስመ ኢኮነ ጊዜሁ ለሐኒጽ - ለማነጽ ወቅቱ አልረዳንም" እያሉ ቤተ መቅደሱ ሳይታነጽ ዘመናት አለፉ:: የሚገርመው ግን ቤተ መቅደሱ ምድረ በዳ ሆኖ የራሳቸውን ቤት አሳምረው ያንጹ ነበር::
+በዚህ ጊዜ በመካከላቸው የነበረው ቅዱስ ሐጌ ዘለፋቸው::
"እምጊዜሁ ለክሙ ከመ አንትሙ ትንበሩ ውስተ ቤት ጥፉር: ወቤትየሰ ምዝቡር? - ቤቴ ፈርሶ ሳለ እናንተ ባማሩ ቤቶቻችሁ ልትኖሩ ጊዜው ነውን?" (ሐጌ. 1:4) አላቸው::
+አክሎም "ቃላችሁን አልፈጸማችሁምና በረከቴን ከእናንተ አርቃለሁ" አላቸው:: ተግሣጹን ከልብ የሰሙት ሕዝቡም በዘሩባቤል መሪነት 46 ዓመታት የፈጀውን ቤተ መቅደስን አንጸዋል::
+ቅዱስ ሐጌም በሕጉ እየኖረ: ትንቢትን እየተናገረ ዘመኑን ፈጽሟል:: በትውፊት ትምሕርትም ቅዱሱ የተወለደው በ500 ዓ/ዓ ሲሆን ያረፈው በ70 ዓመቱ በ5,070 ዓ/ዓ ነው:: ከክርስቶስ ልደት 430 ዓመታት በፊት ማለት ነው::
=>አምላከ ሐጌ ለቤቱ የምናስብበትን ዘመን ያምጣልን:: ከቅዱሱ ነቢይ በረከትም ይክፈለን::
1.ቅዱስ ሐጌ ነቢይ
2.አባ አውጋንዮስ
3.ታውፊና ንግሥት
=>ወርኀዊ በዓላት
1..ቅዱስ ዮሐንስ ሐፂር
2.ቅዱስ አክሎግ ቀሲስ
3.ቅዱስ አፄ ካሌብ ጻድቅ (ንጉሠ ኢትዮዽያ)
4.አባ አሞንዮስ ዘሃገረ ቶና
5.ቅድስት ሳድዥ የዋሒት
6.ማር ቴዎድሮስ ኃያል ሰማዕት
=>+"+ 'ብሩ የእኔ ነው:: ወርቁም የእኔ ነው' ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር:: 'ከፊተኛው ይልቅ የዚህ የሁለተኛው ቤት ክብር ይበልጣል' ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር:: በዚህም ሥፍራ ሰላምን እሰጣለሁ:: +"+ (ሐጌ. 2:9)
<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††
†††✝️ ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት ✝️†††
††† በቤተ ክርስቲያን ክቡር ከሆኑ ሊቃነ መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ገብርኤል ብዙ የክብር ስሞች አሉት:: በተለይ ግን:-
*ሊቀ አርባብ:
*መጋቤ ሐዲስ:
*መልአከ ሰላም:
*ብሥራታዊ:
*ዖፍ አርያማዊ:
*ፍሡሐ ገጽ:
*ቤዛዊ መልአክ:
*ዘአልቦ ሙስና . . . እየተባለ ይጠራል::
በብሉይ ኪዳንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን ስሙ በብዛት ተጠቅሷል:: ስለ ረዳትነቱና አማላጅነቱም ቤተ ክርስቲያን በስሙ ታቦት ቀርጻ: መቅደስ አንጻ በሥርዓት ክብሩን ትገልጻለች::
ከእነዚህም አንዱ ሠለስቱ ደቂቅን እንዳዳነ የሚታሰብበት አንዱ በዓሉ ዛሬ ነው::
"ለዝንቱ ዜናዊ መልአከ ኃይል::
በዛቲ ዕለት ከመ ይትገበር በዓል::
መምሕራን አዘዙ ወሠርዑ በቃል::" እንዲል:: (አርኬ)
ንጉሡ ከምርኮ ወጣቶች ለቤተ መንግስት ሲመርጥ ሦስቱ ቅዱሳንና ዳንኤል ተመርጠው የምቾት ሕይወት ተዘጋጅቶላቸው ነበር:: ነገር ግን በምግብና በአምልኮ ከአሕዛብ ጋር መተባበርን አልፈለጉምና ምርጫቸው ጾምና ጸሎት ከቆሎ ጋር ሆነ::
ምንም እንኳ በቤተ መንግስት ውስጥ ቢኖሩ: ምንም የነገሥታት ልጆች ቢሆኑ ለእነርሱ ከእግዚአብሔር ፍቅር የተሻለ አልነበረምና በጥሬ ቆሎ ተወስነው ኖሩ::
አምላካቸው ከሃሊ ነውና በውበትም ሆነ በጥበብ በባቢሎን ምድር ከነርሱ የሚደርስ አልተገኘም:: ንጉሡም በባቢሎንና በአውራጃዋ ላይ ሾማቸው:: ስማቸውንም በአማልክቱ ስም ሲድራቅ: ሚሳቅና አብደናጐ አላቸው::
ከነገር ሁሉ በኋላ አሕዛብ ቀንተውባቸዋልና የክፋት አዋጅን አሳወጁ:: ናቡከደነጾር 60 ክንድ ቁመት ያለውን የወርቅ ምስል አቁሞ ስገዱ ቢላቸው አይሆንም በማለታቸው ተቃጥለው እንዲሞቱ እሳት ተፈረደባቸው:: ነበልባሉ ከጉድጓዱ ወደ ላይ 49 ክንድ ቢነድም ቅንጣት ያህል ፍርሃት አልጎበኛቸውም::
ወደ እሳቱም ሲጥሏቸው መልዐከ አድኅኖ ቅዱስ ገብርኤል ደርሶ አዳናቸው:: ከሆነው ነገር የተነሳ አሕዛብ አፈሩ:: ናቡከደነጾር ግን ከዙፋኑ ተነስቶ የቅዱሳኑን አምላክ እግዚአብሔርን ባረከ::
ቅዱሳኑን ያዳነ ቅዱስ መልአክ እኛንም ያድነን ዘንድ እንደ አባቶቻችን
"አድኅነኒ ዘአድኃንኮሙ በአክናፊከ ምንትው::
አመ ውስተ እሳት ተወድዩ ሠለስቱ እደው::" እያልን እንለምነው:: (መልክዐ ገብርኤል)
††† ✝️ቅዱስ ዮሐንስ ዘቡርልስ✝️ †††
††† ይህ ቅዱስ አባት ስም አጠራሩ የከበረ ነው:: ሊቅም: ጻድቅም: ጳጳስም: ገዳማዊም ነው:: ከሁሉም በላይ ግን ዛሬም ድረስ ቤተ ክርስቲያን በተድላ ለምትጠቀምባቸው መጻሕፍት (ስንክሳር: ግጻዌ እና ሃይማኖተ አበው) መሠረትን የጣለ ቅዱስ ሰው ነው::
ቅዱስ ዮሐንስ በትውልዱ ግብጻዊ ሲሆን ጊዜውም 5ኛው መቶ ክ/ዘ ነው:: ወላጆቹ ክርስቲያኖች: በዚያውም ላይ ሞልቶ የተረፋቸው ባለ ጠጐች ነበሩ:: እንደ ሕጉ ወጣት እስኪሆንና ራሱን እስኪችል ድረስ አሳደጉት::
ከዚያ ግን ድንገት አባቱና እናቱ ተከታትለው ዐረፉ:: ከቁጥር የበዛ ሃብትን የግሉ ያደረገው ቅዱስ ዮሐንስ ምን እንደሚያደርግበት ጨነቀው:: አንድ ትልቅ ነገር ግን ከማይሆን ጐዳና ጠበቀው::
ወላጆቹ ሁሌም መዝገብን በሰማያት ያገኙ ዘንድ ለነዳያን ይራሩ ነበርና ይህንኑ ለመቀጠል ወሰነ:: መልካም ፍሬ ከመልካም ዛፍ ነውና (ማቴ. 7:16) ወላጅ ለልጁ ማውረስ ያለበት ምድራዊ ሃብትን ሳይሆን በጐ ሕሊናን ነው:: ሳይሠሩ ያገኙት ሃብት ብዙዎችን አጥፍቷቸዋል::
ለዛም ይመስላል ዛሬ አንዳንዶቻችን በቤተሰቦቻችን ሃብት ከእኛ አልፈን ትውልዱን እየገደልንበት ያለው:: ለዚህ ደግሞ እግዚአብሔር ንስሃ ካልገባን ይመጣብናል:: መቅረዛችን (ሕይወታችንም) ከእኛ ላይ ይወስዳል::
ፍርድ የሚሆነው በክፉው ትውልድ ላይ ብቻ አይደለም:: ይህንን ትውልድ በፈጠርነውና መልካሙን መንገድ ባልመራነው በሁላችንም ላይ እንጂ:: (ራዕ. 2:5)
ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ቅዱስ ዮሐንስ በወላጆቹ ሃብት የእንግዶች ማረፊያ የሚሆኑ ቤቶችን አንጾ ነዳያንን ይንከባከብ ገባ:: ሙሉውን ቀን ለነዳያን ሲራራ ይውላል:: አመሻሽ ላይ እንግዶችን ተቀብሎ: አብልቶ ያሳርፋል::
ከዚያም ፈጣሪውን ያመሰግናል:: በእንዲህ ያለ ሕይወት ዘመናትን ካሳለፈ በኋላ አንድ እንግዳ መነኮስ ወደ ቤቱ መጣ:: አስተናግዶት ሲጨዋወቱ አደሩ:: ሌሊት ላይ ግን ስለ ምንኩስና ሕይወትና ስለ ክብሩ ነግሮት ነበርና ልቡ ተመሰጠ::
መነኮሱን ከሸኘው በኋላም ይመንን ዘንድ ቆረጠ:: ነዳያንን ሰብስቦ ሃብቱን አካፈላቸው:: ከዚያም ወደ ገዳመ አስቄጥስ ሒዶ የታላቁ አባ ዳንኤል ደቀ መዝሙር ሆነ:: በትሕትና ለአባቶች እየታዘዘ ከቆየ በኋላ በጭንቅ ደዌ ተያዘ:: ሰይጣን በቅንዓት ገርፎት ነበርና::
እርሱ ግን በደዌው ምክንያት ለዓመታት መሬት ላይ ወድቆ ቢቆይም ፈጣሪውን ፈጽሞ ያመሰግን ነበር:: እግዚአብሔር ደግሞ በፈውስና በኃይል አስነሳው::
በጊዜው የቡርልስ ጳጳስ ዐርፎ ነበርና አባት ፍለጋ ወደ አስቄጥስ ገዳም መጥተው ነበር:: መንፈስ ቅዱስ መርጦታልና አበው ቅዱስ ዮሐንስ ጳጳስ ይሆን ዘንድ አስገደዱት:: እርሱም የፈጣሪ ፈቃድ መሆኑን ስላወቀ ሔደ::
በዚያም (በሃገረ ቡርልስ) ታላቁን ገድል ተጋደለ:: ወደ ከተማዋ ሲገባ ብዙ ነገሮች ከሚገባው ሥርዓት የወጡ ነበሩ:: ብዙ ሰው የእግዚአብሔርን ድምጽ ከመስማት ይልቅ ባላስፈላጊ ነገሮች ላይ ተጠምዶ ነበርና መንጋውን ያድን ዘንድ ተጋ::
ሳይሆኑ "ባሕታዊ": "አጥማቂ" ነን እያሉ ሕዝቡን የሚያሳስቱ ተኩላዎችንም አስወገደ:: ለሕዝቡ አጉል ሕልም: ሟርትን የሚያስተምሩትን ገሠጸ:: አንመለስም ያሉ መናፍቃንን እሳት ከሰማይ ወርዳ በላቻቸው::
ቅዱስ ዮሐንስ ከቅድስናው ብዛት ዘወትር ሲቀድስ መድኃኒታችንንና አእላፍ መላእክትን ያይ ነበር:: ከከዊነ እሳት ማዕረግ በመድረሱም አካሉ በመፈተት ሰዓት እንደ እሳት ይነድ ነበር:: እንባውም እንደ ውኃ ይፈስ ነበር::
ቅዱስ ዮሐንስ ከዚህ ጐን ዛሬም ድረስ የሚታወቅበትን ታላቅ ሥራም ሠርቷል:: መንፈስ ቅዱስ አነሳስቷቸው ቅዱሱና የሃገረ አትሪብ ጳጳስ የነበረው ሊቁ አባ ሚካኤል መጽሐፈ ስንክሳርን : መጽሐፈ ግጻዌንና ሃይማኖተ አበውን ለመጀመሪያ ጊዜ አዘጋጅተዋል::
"ስንክሳር" የቅዱሳንና የፈጣሪን ነገር በየዕለቱ የሚዘግብ መጽሐፍ ሲሆን "ግጻዌ" የየዕለቱን በዓላት ከምስባክና ምንባባት ጋር አስማምቶ የያዘ መጽሐፍ ነው:: "ሃይማኖተ አበው" ደግሞ የዶግማ መጽሐፍ ሆኖ ከሐዋርያት እስከ ሊቃውንት ድረስ የጻፉትን የያዘ ነው:: ሦስቱን የሚያመሳስላቸው "ስብስብ / እስትጉቡዕ / Collection" መሆናቸው ነው::
ቅዱሱ ዮሐንስ በሃገረ ቡርልስ በከፍተኛ ድካም ይህንን ፈጽሞ በዚህች ቀን ዐርፏል::
††† ✝️አቡነ ስነ ኢየሱስ ጻድቅ✝️ †††
*ከምድረ ሽዋ ወደ ታች አርማጭሆ የሔዱ መናኝ:
*ጭው ባለ በርሃ ለቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ ገዳምን ያነጹ አባት:
*ብዙ አርድእትን ያፈሩ መናኝ:
*ብዙ ተአምራትን የሠሩና ወንጌልን ያስተማሩ መነኮስ ናቸው::
በደመናም ይጫኑ ነበር:: ገዳማቸውም (ታች አርማጭሆ: ከሳንጃ ከተማ የ3 ሰዓት መንገድ ይወስዳል) ድንቅና ባለ ብዙ ቃል ኪዳን ነው:: መልአከ ሞት መስከረም 1 ቀን ቢመጣ "የቅዱስ ገብርኤልን በዓል ሳላከብርአይሆንም" ብለው ለ3 ወራት በበራቸው አቁመውታል:: ታኅሣሥ 19 ቀንም ዐርፈዋል::
††† አምላከ ቅዱሳን በመልአኩ ረድኤት ጠብቆ ለጻድቃኑ በረከት ያብቃን::
††† ታኅሣሥ 19 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ዮሐንስ ዘቡርልስ
3.አቡነ ስነ ኢየሱስ ጻድቅ
††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት
2.አቡነ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ
3.አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም
4.ቅዱስ ይምርሐነ ክርስቶስ
††† ". . . በአምላኬም በእግዚአብሔር ፊት ስለ ተቀደሰው ስለ አምላኬ ተራራ ስለምን: ገናም በጸሎት ስናገር አስቀድሜ በራእይ አይቼው የነበረው ሰው ገብርኤል እነሆ እየበረረ መጣ:: በማታም መሥዋዕት ጊዜ ዳሰሰኝ:: አስተማረኝም . . ." †††
(ዳን. ፱፥፳)
††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
🔵TELEGRAM 🔴 YOUTUBE
+*" ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ "*+
=>ከ12ቱ ቅዱሳን ሐዋርያት አንዱ የሆነው ቅዱስ ቶማስ ብዙ መከራን በማሳለፉና የጌታችንን ጐን በመዳሰሱ ይታወቃል::
+ቅዱስ ቶማስ እንደ ሌሎቹ ሐዋርያት በእሥራኤል ተወልዶ በዚያውም በሥርዓተ ኦሪት አድጐ ገና በወጣትነቱ የሰዱቃውያንን ማሕበር ተቀላቅሏል:: ሰዱቃውያን ሰው ከሞተ በሁዋላ አይነሳም (አልቦ ትንሳኤ ሙታን) የሚሉ ናቸው:: መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማስተማር ሲጀምር ግን ቅዱስ ቶማስ ከነበረበት ማሕበር ወጥቶ ጌታችንን ተከተለ:: ጌታችንም ከ12ቱ ሐዋርያት አንዱ ይሆን ዘንድ ሾመው:: የቀደመ ስሙ "ዲዲሞስ" ሲሆን ጌታችን "ቶማስ" ብሎታል::
+ቅዱስ ቶማስ ጌታ አልዓዛርን ለማስነሳት በሔደ ጊዜ ሌሎች ሐዋርያት ጌታን "አይሁድ ይገድሉሃል ቅር" ሲሉት እርሱ ግን "እንሒድና አብረን እንሙት" ሲል ፍቅሩን አሳይቷል:: (ዮሐ. 11:16)
+ጌታችን ትንሳኤውን ለደቀ መዛሙርቱ በገለጠ ጊዜ ያልነበረው ቶማስ ካላየሁ አላምንም አለ:: ምክንያቱም:-
1.ለጌታችን ከነበረው ፍቅር የተነሳ እውነት አልመስልህ ቢለው::
2.አንድም "ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሳኤውን አየን እያሉ ሲያስተምሩ እኔ ግን ሰማሁ ብየ ማስተማሬ ነው" ብሎ በማሰቡ ነበር::
+ለጊዜው ጌታ ተገልጾ ቢገስጸው "እግዚእየ ወአምላኪየ (ጌታየና አምላኬ)" ብሎ ፍጹም ሃይማኖቱን ገልጿል:: ለፍጻሜው ግን የጌታችንን ጎን (መለኮትን) ይዳስስ ዘንድ ባለቤቱ እንዳደለው ያጠይቃል:: መለኮትን የዳሰሰች ይሕቺ ቅድስት እጁ ዛሬም ድረስ ሕያው ናት::
+ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው ሐገረ ስብከት ሲከፋፈሉ ለቅዱስ ቶማስ ሕንድና በዙሪያዋ ያሉ ሃገራት ደረሱት::
+ከዚህ በሁዋላ ነው እንግዲህ ዘርዝረን የማንጨርሰውን ተጋድሎ የፈጸመው:: ቅዱሱ በነበረው ፍጹም ትጋት አባቶቻችን "ዘአሠርገዋ ለብሔረ ሕንደኬ (ሕንድን በወንጌል ያስጌጣት)" ሲሉ ያከብሩታል::
+ቅዱስ ቶማስ ንጉሥ ሉክዮስንና የሃገሩን ሕዝብ ለማሳመን በችንካር መሬት ላይ ወጥረው ቆዳውን ገፈውታል:: ቆዳውንም እንደ ገና ሰፍተው: አሸዋ ሞልተው አሸክመውታል:: በየመንገዱ የተገፈፈ ገላውን ጨው ቢቀቡት በጎች መጥተው ግጠው በልተውታል:: በዚሕ ምክንያት:-
"ኩሉ የአኪ እንዘ የአኪ ዘመኑ::
አባግዒሁ ለቶማስ እስመ አራዊተ ኮኑ::" ብለዋል ሊቃውንቱ::
+በሁዋላ ግን ከፎቅ ወድቃ የሞተችውን የንጉሡን ሚስት በተገፈፈ ቆዳው በማዳኑ ሁሉም አምነው ተጠምቀዋል::
+ቅዱሱ ሐዋርያ ልክ እንደ ቅዱስ ዻውሎስ አንዳንዴ በፈሊጥ: ሌላ ጊዜም በመከራ ለወንጌልና ለቤተ ክርስቲያን ተጋድሏል:: ያለ ማቁዋረጥም ከሕንድ እስከ ሃገራችን ኢትዮዽያ ድረስ ለ38 ዓመታት ወንጌልን ሰብኩዋል:: በመጨረሻም በ72 ዓ/ም በሰማዕትነት አርፏል:: መቃብሩና ቅድስት እጁ ዛሬ ድረስ ሕንድ ውስጥ አሉ:: ከኘሮቴስታንቶች በቀር መላው ዓለም ያከብረዋል:: ዛሬ የቅዱሱ ሐዋርያ በዓለ ፍልሠቱ ነው::
+*" ቅዱስ ቲቶ ሐዋርያ "*+
=>የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር ቅዱስ ቲቶ ከ72ቱ አርድእት አንዱ ሲሆን በተወሰነ መንገድም ቢሆን የተዘነጋ ሐዋርያ አይደለም:: በተለይ ደግሞ ቅዱስ ዻውሎስ ከጻፋቸው 14 መልእክታት መካከል አንዷ የተላከችው ለዚህ ቅዱስ በመሆኗ ታሪኩ እንኩዋ ባይነገር ስሙ አይረሳም:: ቅዱስ ዻውሎስም በመልዕእክታቱ በጐ ስሙን እየደጋገመ ያነሳዋል::
=>ለመሆኑ ሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ማን ነው?
+ቅዱስ #ቲቶ የተወለደው በ1ኛው መቶ ክ/ዘ እስያ ውስጥ ቀርጤስ በምትባል ከተማ ነው::
+መዳን በእውቀት ይመስላቸው ስለ ነበር የአካባቢው ሰዎች የግሪክን ፍልስፍና ጠንክረው ይማሩ ነበር:: ቅዱስ ቲቶም በወጣትነቱ ወደ ት/ቤት ገብቶ የግሪክን ፍልሥፍናና የዮናናውያንን ጥበበ ሥጋ ተማረ:: በጥቂት ጊዜም የሁሉ የበላይ ሆነ::
+ቅዱሱ ምክንያቱን ሳያውቀው ለእኔ ቢጤዎች ያበላ: ያጠጣ: ይንከባከባቸውም ነበር:: እግዚአብሔር ግን የዚህ ቅን ሰው በጐነቱ እንዲሁ እንዲቀር አልወደደምና አንድ ቀን በራዕይ ተገለጠለት::
+በራዕይም አንድ ምንነቱን ያልተረዳው ነገር "ቲቶ ሆይ! ስለ ነፍስህ ድኅነት ተጋደል:: ይህ ዓለም ኃላፊ ነው" ሲለው ሰማ:: ከእንቅልፉ ነቅቶ በእጅጉ ደነገጠ:: የሚያደርገውንም አጣ:: ያናገራቸው ሁሉ ምንም ሊገባቸው አልቻለም::
+ድንገት ግን በዚያ ሰሞን ከወደ ኢየሩሳሌም አዲስ ዜና ተሰማ:: "ክርስቶስ የሚሉት ኢየሱስ: እርሱም የባሕርይ አምላክ የሆነ ወደ ምድር ወርዶ: ስለ እግዚአብሔር መንግስትም እየሰበከ ነው" ሲሉ ለቲቶ ነገሩት::
+"ሌላስ ምን አያችሁ?" አላቸው:: "በእጆቹ ድውያን ይፈወሳሉ: ሙታን ይነሳሉ: እውራን ያያሉ: ለምጻሞች ይነጻሉ: ሌሎች ብዙ ተአምራትም እየተደረጉ ነው" አሉት:: የወቅቱ የሃገረ አክራጥስ መኮንን ፈላስፋ ነበርና ስለ ክርስቶስ ሲሰማ ሊመራመር ወደደ::
+"ብልህ ጥበበኛ ሰው ፈልጉልኝ" ብሎ ተከታዮችን ቢልካቸው ከቲቶ የተሻለ በአካባቢው አልነበረምና እርሱኑ አመጡት:: መኮንኑ ቲቶን "ነገሩ ትክክል ወይም ስሕተት መሆኑን በጥልቅ መርምረህ ምላሽ አምጣልኝ" ብሎ ላከው::
+ቅዱስ ቲቶም ፈጥኖ ተነስቶ ወደ ኢየሩሳሌም ገሰገሰ:: ወደ ከተማዋ እንደገባም ጌታችንን አፈላልጐ አገኘው::
1.ጌታችን ክርስቶስ በሥልጣነ ቃሉ ደዌያትን ሲያርቅ: አጋንንትን ሲያሳድዳቸው ተመልክቶ ይህ ሥራ የፍጡር እንዳልሆነ ተረዳ::
2.ጌታችን የሚያስተምረው ትምሕርት ከግሪክ ፍልሥፍና እጅግ ርቆና መጥቆ አገኘው:: ጌታ በጣዕመ ቃሉ የሚያስተምረው ሰማያዊ: በዚያ ላይ ዘለዓለማዊ የሆነ ትምሕርት ነው:: በራዕይ "ስለ ነፍስህ ተጋደል" ያለው ምሥጢር አሁን ተተረጐመለት::
+በዚህ ምክንያትም ጊዜ አላጠፋም:: ወዲያውኑ አምኖ ተከታዩ ሆነ:: ጌታም ከ72ቱ አርድእት ደመረው:: የአክራጥስ መኮንን "ምነው ዘገየህ?" ቢለው ያየውን ሁሉ ጽፎ: እንደማይመለስም አክሎ ደብዳቤ ላከለት::
+ከዚህ በሁዋላ ቅዱስ ቲቶ ከጌታችን እግር ለ3 ዓመታት ተምሮ: በበዓለ ሃምሳ መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ: በመላው እስያ ወንጌልን ሰብኩዋል:: ቅዱስ ዻውሎስ ባመነ ጊዜ ደግሞ የእርሱ ደቀ መዝሙር ሆኖ ለ25 ዓመታት አስተምሯል::
+ቅዱስ ዻውሎስ ሰማዕት ከሆነ በሁዋላ ደግሞ ወደ አክራጥስ ተመልሶ: ሕዝቡን አሳምኖና አጥምቆ: ቤተ ክርስቲያንን አንጿል:: ዕድሜው በደረሰ ጊዜም መምሕራንን: ካህናትን ሹሞላቸው: ባርኩዋቸውም ዐርፏል:: ዛሬ የቅዱሱ ሐዋርያ በዓለ ፍልሠቱ ነው::
+*" አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን "*+
=>ቅዱሱ በትውልዳቸው ግሪካዊ ቢሆኑም ሶርያ አካባቢ እንዳደጉ ይታመናል:: በቀደመ ስማቸው ፍሬምናጦስ የሚባሉት አቡነ ሰላማ ወደ ኢትዮዽያ የመጡት በአደጋ ምክንያት ቢመስልም ውስጡ ግን ፈቃደ እግዚአብሔር ነበረበት::
+በድንበር ጠባቂዎች ከባልንጀራቸው ኤዴስዮስ ጋር ተይዘው ወደ አክሱም የመጡት በንጉሥ ታዜር (አይዛና) እና በሚስቱ ሶፍያ (አሕየዋ) ዘመን ነው:: ጊዜው በውል ባይታወቅም በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው::
Reviews channel
- Added: Newest first
- Added: Oldest first
- Rating: High to low
- Rating: Low to high
Catalog of Telegram Channels for Native Placements
Advertising on the Telegram channel «ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan» is a Telegram channel in the category «Религия и духовность», offering effective formats for placing advertising posts on TG. The channel has 13.4K subscribers and provides quality content. The advertising posts on the channel help brands attract audience attention and increase reach. The channel's rating is 27.5, with 1 reviews and an average score of 5.0.
You can launch an advertising campaign through the Telega.in service, choosing a convenient format for placement. The Platform provides transparent cooperation conditions and offers detailed analytics. The placement cost is 30.0 ₽, and with 1 completed requests, the channel has established itself as a reliable partner for advertising on Telegram. Place integrations today and attract new clients!
You will be able to add channels from the catalog to the cart again.
Комментарий